የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ: የትምህርት ሚኒስቴር እና የሲዳማ ክልል ትምህርት ቢሮ የስራ ኃላፊዎች በወንዶ ገነት ወረዳ ጩኮ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ተገኝተው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ አከናውነዋል::
በኢፌዲሪ ትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ት/ት ዘርፍ ሚኒስትር ደኤታው ክቡር ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ ከችግኝ ተከላው መርሃግብር መልስ ለጩኮ የመ/ደ/ት/ቤት ተማሪዎች እና ለወንዶገነት ወረዳ ትምህርት ቢሮ የትምህርት መርጃ ቁሳቁስ ድጋፍ አበርክተዋል::
ዶ/ር ሳሙኤል ትምህርት ለአሁናዊ የዓለም ሁኔታ የሚመጥን ትውልድ የሚፈራበት ታላቅ አገራዊ ተልዕኮና ቴክኖሎጂና ስልጣኔን የታጠቀ ትውልድ የሚፈጠርበት መንገድ ነው ካሉ በኃላ የዕለቱ የአረንጓዴ አሻራ ፕሮግራም በክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴሩ የተጀመረው የክረምት በጎ አድራጎት አካል መሆኑን አስታውሰዋል:: በዚሁ መርሃግብር ላይ ትውልድን ለመቅረፅ የሚደረገውን ርብርብ በመደገፍ ወጣቱንና የነገ ሃገር ተረካቢውን ትውልድ ሌሎችን በመደገፍ ከራሱ በላይ ለሌሎች በመኖር የሚገኘውን ደስታ እንደ እሴት ይዞ እንዲገነባ አስተዋፅኦ ይኖረዋል ብለዋል:: አክለውም ይሄንን ድንቅ አላማ ትምህርት ሚኒስቴር ብቻውን የሚያሳካው ሳይሆን ሁሉም ባለድርሻ አካላት በህብረት ተሳትፎ ሲያደርጉ እንደሆነ ጠቁመው ሐዋሳ ዩኒቨርሲቲና የክልሉ ተወላጆች እንደ ባለድርሻ አካላት ይሄንን ታላቅ አላማ ለመደገፍ ቀድም ብሎ ከተጀመረው ድጋፍ ባሻገር የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንደሚያደርጉ ያላቸውን ጠንካራ እምነት ገልፀዋል:: በመጨረሻም ለወረዳው ት/ቢሮ 20 ዴስክቶፕ ኮምፒዩተሮች ያበረከቱ ሲሆን ለጩኮ የመ/ደ/ት/ቤት ተማሪዎች ደግሞ 3500 መፃህፍት: 700 የሴት ተማሪዎች የንጽህና መጠበቅያ ሞዴስ: እንዲሁም 1000 የተማሪ ቦርሳዎችን አበርክተዋል::
የክልሉ ምክ/ር/መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ክቡር አቶ በየነ በራሳ እና የወንዶ ገነት ከተማ ከንቲባ ለተደረገው ድጋፍ ለትምህርት ሚኒስቴር ምስጋና አቅርበዋል::