በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የ12ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ ፈተና ለሚወስዱ ተማሪዎች ገለፃ ተሰጠ::
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ዘንድሮ ለሁለተኛ ግዜ በዩኒቨርሲቲ የሚሰጠውን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ማጠናቀቂያ ፈተና ለሚወስዱ 15,503 የተፈጥሮ ሳይንስ ዘርፍ ተፈታኝ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው የአስተዳደርና ተማሪዎች ጉዳይ ም/ፕሬዚደንት ዶ/ር ሳሙኤል ጂሎና ከትምህርት ሚኒስቴር በመጡ የክላስተር አስተባባሪዎች የዩኒቨርሲቲ ቆይታና የፈተና አሰጣጥ ስነ ሥርዓት ላይ ማብራሪያ (ኦሪየንቴሽን) ተሰጥቷል::
የአስ/ተ/ጉ/ም/ፕሬዚደንት ዶ/ር ሳሙኤል ጂሎ ተማሪዎቹን እንኳን ወደ ዩኒቨርሲቲያችን በደህና መጣችሁ ካሉ በኃላ ተማሪዎች ዩኒቨርሲቲው ውስጥ በሚኖራቸው ቆይታ ሁሉንም የካምፓስ አስተዳደር ህግጋት ተረድተው ውጤታማ እንዲሆኑ ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ: አላስፈላጊ የስነ ምግባር ጉድለት እንዳያሳዩ: ተረጋግተው ፈተናቸውን እንዲሰሩ: ያልተፈቀዱ ምንም አይነት ነገሮችን እንዳይፈፅሙ: ምክር ሰጥተዋል:: በማስከተልም ዩኒቨርሲቲው የራሳቸው ቤት እንደሆነ ተረድተው በቆይታቸው የሚያጋጥማቸውን ማንኛውም አስቸጋሪ ሁኔታ ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት በቶሎ እንዲያሳውቁና እንደቤታቸው ነፃ ሆነው እንዲኖሩ ነግረዋቸዋል:: ምክትል ፕሬዚደንቱ አክለውም ሁሉም የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ የእናንተን ደህንነት ጠብቀን በሰላማዊ ሁኔታ ተፈትናችሁ ለመልካም ውጤት እንድትበቁ አስፈላጊውን ሁሉ ኃላፊነት እንወጣለን ብለዋል::