የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትሩ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የኢኖቬሽን ቴክኖሎጂን የምርምር እና የፈጠራ ውጤቶችን ጎበኙ።
የትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትሩ ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ እና ሌሎችም ከፍተኛ አመራር አካላት ከተጀመረው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባኤ ጎን ለጎን በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የተሠሩ ሥራዎችን ሲጎበኙ የኢኖቬሽን ቴክኖሎጂን የምርምርና የፈጠራ ውጤቶችን መመልከት ችለዋል፡፡
የህብረተሰቡን ችግሮች ለመፍታት እንዲቻል በየዘርፉ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ከዩኒቨርሲ የሚጠበቅ ቁልፍ ተግባር መሆኑ ታምኖ ባሁኑ ጊዜ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በዚህ ረገድ አመርቂ ሥራዎች እየተሠሩ ይገኛሉ፡፡ መተላለፍ አለባቸው፡፡ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በቴክኖሎጂ ሽግግር እና የዩኒቨርስቲ-ኢንዱስትሪ ትስስር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ባዩ ቡንኩራ ሲገልጹ ወጣቱ ትውልድ እውቀቱን፣ ተሰጥኦውን ወይም የፈጠራ ሀሳቡን ወደ ንግድ ሥራ እንዲቀይር፣ የራሱን ኢንተርፕራይዝ እንዲፈጥር እና ሌሎችን በስራ እድል ተጠቃሚ እንዲያደርግ የኢኖቬሽን ስነ-ምህዳር እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል፡፡ ይህን ባገናዘበ ሁኔታ ዳይሬክቶሬቱ በየዓመቱ ቴክኖሎጂዎችን በተማሪዎች እና በመምህራን በማበልጸግ ወደ ኢንዱስትሪዎች በማስተላለፍ ላይ ይገኛል ብለዋል ዳይሬክተሩ፡፡
አክለውም ከዚህ ቀደም በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ባዘጋጀው 3ኛው አገር አቀፍ የትምህርት ኮንፍረንስ ላይ ባለፉት ሶስት አመታት ከተዘጋጁት ቴክኖሎጂዎች ከ20 ያላነሱ ለእይታ መቅረባቸውን የገለጹት ዶ/ር ባዩ ቡንኩራ ከእነዚህ ቴክኖሎጂዎች መካከል ዘመናዊ የዶሮ መፈልፈያ እንኩቤተሮች፣ የሃይድሮሊክ ላብራቶሪ ማስተማሪያ ማሽኖች፣ አነስተኛ መስኖ ያለ ፓምፕ ማሽኖች፣ ኃይል ቆጣቢ የነዳጅ ምድጃዎች፣ ወዘተ እንደሚገኙበት ዘርዝረዋል፡፡ ቀጥለውም ባስተላለፉት መልዕክት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሁሉም ንቁ ወጣት ዜጎች ዋና መድረሻና የእውቀት ማዕከል በመሆናቸው ወጣቶች የፈጠራ ሀሳባቸውን፣ እውቀታቸውን እና ልዩ ክህሎቶቻቸውን በተግባር እንዲያሳዩ የሚያስችል የፈጠራ ስነ-ምህዳር ሊኖራቸዉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።