የአዋዳ ቢስነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ የ2014 በጀት ዓመት የ12 ወር ዕቅድ አፈፃፀም ላይ ውይይት አደረገ፡፡
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የአዋዳ ቢስነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ በ2014 በጀት ዓመት የ12 ወር ዕቅድ አፈፃፀም ላይ በሰኔ 29/2014ዓ.ም ውይይት እና ግምገማ አድርጓል፡፡
የአዋዳ ቢስነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ዲን ዶ/ር ወገኔ ማርቆስ በመክፈቻው ላይ እንደገለፁት እንደሚታወቀው የበጀት ዓመቱን ስንጀምር ምን መስራት እንዳለብን በዕቅዳችን ላይ ተወያይተን ሲሆን የዓመቱን ዕቅድ አፈፃፀምንም በየሩብ ዓመቱ እየገመገምን የመጣን ቢሆንም በዛሬው ዕለት የዓመቱን ክንውኖች ጠቅለል በማድረግ በስኬቶቻችን እና በክፍተቶቻችን ላይ ውይይትና ግምገማ ለማድረግ የተዘጋጀ መድረክ ነው ብለዋል፡፡
ዶ/ር ወገኔ አክለውም በዓመቱ በርካታ ስራዎችን ያከናወንን ሲሆን አፈፃፀማችንም አሳታፊ ነበር በማለት አዳዲስ ሁለት የሶስተኛ ድግሪ የትምህርት ፕሮግራሞችን የከፈትን እና በቀጣይም ሁለት የሶስተኛ እና ሁለት የሁለተኛ ድግሪ ፕሮግራሞችን ለመክፈት በዝግጅት ላይ ስንሆን ከውጪ ሀገራት እና በሀገር ውስጥ ካሉ ባለድርሻ አካለት ጋርም መግባቢያ ሰነዶችን በመፈራረም እየሰራን እንገኛለን ብለዋል፡፡
በኮሌጁ የመማር ማስተማሩን ሂደት የተሻለ ለማድረግ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ እና ቤተመፃህፍቶቹንም ዲጅታል መደረጋቸውን፣ የመኪና ጋረዥና ማጠቢያ መዘጋጀቱን፣ የተማሪዎች ምግብ ማብሰያውም በዘመናዊ መልኩ ግብዓቶች ተሟልተው መደራጀቱን እንዲሁም የሰው ሃብትን በተመለከተም መረጃዎች ተሰብስበው ዲጅታላይዝ መደረጋቸውን ዲኑ ገልፀው ከዚህ ግምገማም በመነሳት በቀጣይ ዓመት ያልተሰሩ ስራዎችን በዕቅዳችን አካተን ለመስራት፣ የመውጫ ፈተና ለተመራቂዎች ስለሚሰጥ ተማሪዎች ውጤታማ እንዲሆኑ መምህራን ተማሪዎች የማስታወስ ክህሎታቸውን የሚያሳድጉ የትምህርት አሰጣጥ እና የመመዘኛ ፈተናዎች ላይ እንዲያተኩሩ እንደሚደረግ እና ለተማሪዎችም የመርጃ መፅሀፍቶች በተሟላ መልኩ ዲጅታል ተደርገው እንዲቀርቡ እንደሚደረግ ገልፀው መምህርና እና ሰራተኞች የያዝነውን ዓላማ ከግብ ለማድረስ በዘንድሮ ዓመት ያሳዩትን ቁርጠኝነት በቀጣይም በተሻለ እንዲፈፅሙት አደራ እያልኩኝ ለኮሌጁ ስኬት ድጋፍ ላደረጉ ለዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ ለኮሌጁ መምህራኖች እና የአስተዳደር ሰራተኞች የላቀ ምስጋናዬን አቀርባለሁኝ ብለዋል፡፡