በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ አንጋፋ የሆነው የግብርና ኮሌጅ በ2014ዓ.ም የመጀመሪያው 6 ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ላይ በጥር 4/2014 ዓ.ም ግምገማና ውይይት አካሄደ፡፡
ዶ/ር ታረቀኝ ዮሴፍ የግብርና ኮሌጅ ዲን በግምገማው መክፈቻ ላይ እንደገለፁት መንግስት የከፍተኛ ት/ት ጥራትን፣ ተደራሽነትንና አግባብነትን ለማሳደግ በዘርፉ የሰጠውን ልዩ ትኩረት ለማስቀጠልና የዩኒቨርሲቲውን ተልዕኮ ሊያሳካ በሚችል አግባብ ዓመታዊ ዕቅድ አዘጋጅቶ መተግበር የሚያስፈልግ በመሆኑ ኮሌጃችን የአስር ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ በማዘጋጀት ወደ ስራ የገባ ሲሆን ይህም ዕቅድ በእያንዳንዱ ዓመት ተሸንሽኖ እየተተገበረ ይገኛል ብለዋል፡፡
የኮሌጁ ዲን ቀጥለው እንደተናገሩትም በኮሌጃችን በመማር ማስተማሩ፣ በምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ዘርፍ አበረታች ውጤቶች የተመዘገቡና በቀጣይ ዓመታትም ጠንክረን መስራት ከቻልን የተሻለ አፈፃፀም የሚመዘገብበት ሰፊ ዕድል ያለ መሆኑ አመላካች ሁኔታዎች መኖራቸውን ጠቅሰው ባለፉት ዓመታት የተመዘገበውን ውጤት አጠናክሮ ከማስቀጠል አንፃርም የክትትልና ግምገማ ስርዓታችንን በማጠናከር በየሩብ ዓመቱ የአፈፃፀም ሪፖርት ከፋካሊቲዎች፣ ት/ቤቶችና ስራ ሂደቶች የሚቀርቡበት መድረኮች ተጠናክረው የሚቀጥሉ ይሆናል ብለዋል፡፡
በዕለቱም ከፋካሊቲዎች፣ ት/ቤቶችና፣ ስራ ሂደቶች እና የምርምርና ቴ/ሽ/ ተባባሪ ዲን የ 6 ወራት ስራ አፈፃፀም ሪፖርቶች ቀርበው ግምገማና ውይይት ተደርጎባቸው ፕሮግራሙ ተጠናቋል፡፡