በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የወንዶገነት ደንና ተፈጥሮ ሃብት ኮሌጅ በሲዳ ፕሮጀክት ድጋፍ ሲሰሩ የነበሩትን ተግባር ተኮር የምርምርና ጥናት ውጤቶች ላይ ውይይትና ምክክር በህዳር 11/2014ዓ.ም አካሄደ፡፡
ዶ/ር መሰለ ነጋሽ የወንዶገነት ደንና ተፈጥሮ ሃብት ኮሌጅ መምህርና የሲዳ ፕሮጀክት አስተባባሪ እንደገለጹት የዚህ መሰሉ ምርምር ተግባር እና እድገት ተኮር እንዲሁም ማህበረሰቡን አሳታፊ በመሆኑ እና የተለያዩ ተመራማሪዎች ስለሚካፈሉበት ችግሮቹን እና መፍትሄዎቹንም ከተለያዩ ሙያዎች አንፃር ለማየት ስለሚረዳ ለየት ያደርገዋል ብለዋል፡፡
ዶ/ር መሰለ አክለውም ምርምሮቹ የኮሌጁ ደን ሃብት እየተመናመነ በመሆኑ እንዴት እንታደገው እና እንዴትስ ግጭቶችን እንፍታ፣ ኮሌጁ በዙሪያው ከኢኮ-ቱሪዝም አንፃር ምን አለው ካለስ ለማሳደግ በምን መልኩ የአቅም ግንባታ ስራዎች ይሰሩ እንዲሁም የኢኮ ሲስተም አገልግሎትን ከማዘመንና ከማሳደግ አንፃር እንዲሁም በአካባቢው ያለውን የከርሰ ምድር ውሃ ሃብት ምንያህል ነው በሚሉ አንኳር ሃሳቦች ላይ በማተኮርና በደኑ አካባቢ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሁኔታ ያካተተ ምርምር መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በመጨረሻም ምርምሮች የአካባቢውን ማህበረሰብ አካታችና የደኑን ህልውና እንዲያስጠብቅ የኢኮኖሚው ተጠቃሚ በማድረግ መሰራት እንዳለባቸው በውይይቱ ለመረዳት ተችሏል፡፡