የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት በሲዳማ ክልል ሁላ ወረዳ ለሚገኙ አርሶ አደሮች የእርሻ ምርትና ምርታማነት እንዳይቀንስ መንግስት እየሠራ ያለውን ሥራ ለመደገፍ 372 ኩንታል የተለያዩ ምርጥ ዘሮችን በ03/11/12 ዓ.ም አበረከተ፡፡
ዶ/ር አያኖ በራሶ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት በዕለቱ ተገኝተው ዩኒቨርሲቲው በዓለም ደረጃ በተከሰተው በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት ህብረተሰቡ ተጋላጭ እንዳይሆን የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ በመሥራት እንዲሁም የእጅ ንጽህና መጠበቂያ ሳኒታይዘር አምርቶ ተጋላጭ ለሆኑ ህብረተሰብ ክፍሎች በማከፋፈል ጭምር አጋርነቱን ማረጋገጡን ገልጸው ዩኒቨርሲቲው በክልሉ በሚገኙ የተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች በሚገኙ የቴክኖሎጂ መንደሮችና የአርሶ አደሮች ማሳ ላይ የተለያዩ ምርጥ ዘሮችን አምርቶ በማሳየትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ሥራዎችን ከመሥራቱ በተጨማሪ የዚህን መሰሉ የተለያዩ ምርጥ ዘሮችን ለአርሶ አደሮች በማበርከት ምርታማነትን ከፍ ማድረግ እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡
አቶ ካሱ አሩሳ የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ኃላፊ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ ጊዜያት ወደ አርሶ አደሮቻችን በመውረድ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና የአርሶ አደሮችን ኑሮ ለማሳደግ የሚችሉ በምርምር የተገኙ ውጤቶችን እያበረከተና እየሠራ በመሆኑ አመስግነው በዕለቱ የተበረከተው የምርጥ ዘሮችም ውጤታማ እንዲሆኑና ምርትና ምርታማነትን ከፍ ለማድረግ እንዲረዳን ለሁሉም ባለድርሻ አካላት በየደረጃው ስልጠና በመስጠት አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም ከዚህ በፊት ከሚታረሱ መሬቶች በተጨማሪ የሚገኙትን ቦታዎች እንዲያርስ ለማድረግ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ መሥራት ይኖርብናል፡፡